የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ እና የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ በጋራ የሚያከናውኑዋቸውን ተግባራት መሰረት ያደረገ የስምምነት ፊርማ ተፈራረሙ፡፡

by | ዜና

(ቀን ጥር 29/2016 ዓ.ም) የስምምነት ፊርማውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱ እና የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ በላይ ደጀን የተፈራረሙ ሲሆን መርሀ ግብሩ በቅርቡ በከተማ አስተዳደሩ በተደረገ የትምህርት ቤት አመራር ውድድር አልፈው ስልጠና በመውሰድ ላይ የሚገኙ ርዕሳነ መምህራን እና  በየደረጃው የሚገኙ የሁለቱ ተቋማት አመራሮች በተገኙበት ነው የተካሄደው፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱ  በስምምነት ፊርማ መርሀግብሩ ባስተላለፉት መልዕክት በትምህርት ቤቶች የሚካሄድ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በአካልና አዕምሮ የዳበረ  ትውልድ መፍጠር የሚያስችል ተግባር እንደመሆኑ ሴክተሩ ሪፎርም እያካሄደባቸው ከሚገኙ የትኩረት መስኮች መካከል አንዱ  መሆኑን ጠቁመው የትምህርት ቤት አመራሮችም በየትምህርት ቤቱ የሚካሄዱ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን ወጥ በሆነ መልኩ በማካሄድም ሆነ የማዝውተሪያ ስፍራዎቹን ለአከባቢው ማህበረሰብ በተለይም ለወጣቶች ክፍት በማድረግ ወጣቶቹ  ከአልባሌ ቦታ  መታደግ እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ በላይ ደጀን በበኩላቸው ትምህርት ቤቶች የነገ የሀገር ተረካቢ ዜጎችም ሆኑ ተተኪ ስፖርተኞች የሚፈሩባቸው ተቋማት እንደመሆናቸው ቢሮው ከአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ጋር በጋራ በመሆን በትምህርት ቤቶች የሚገኙ የማዘውተሪያ ስፍራዎችን በማስፋፋትም ሆነ በተማሪዎችና መምህራን መካከል ስፖርታዊ ውድድሮችን በማካሄድ ላይ እንደሚገኝ ገልጸው በቀጣይ በሁሉም ትምህርት ቤቶች የሚካሄደው የማለዳ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንዲቀጥልና የስፖርት ሳይንስ መምህራን ሙያዊ ክህሎታቸውን የሚያሳድጉበት ስልጠና እንዲያገኙ በትኩረት የሚሰራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

በመርሀ ግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ዳዊት ትርፉ ባለፉት ሁለት አመታት ሁለቱ ቢሮዎች በጋራ ያከናወኑዋቸው እና በቀጣይ ትኩረት የሚደረግባቸውን ተግባራት አቅርበዋል፡፡

0 Comments

Submit a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *

https://twitter.com/aacaebc

SITE VISITORS

  • 0
  • 119
  • 158
  • 1,412
  • 7,820
  • 235,733
  • 235,733