የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ በተቋሙ የ2016 ዓ.ም አፈጻጸም እና በ2017 ዓ.ም መሪ እቅድ ዙሪያ የክፍለ ከተማ እና ወረዳ ትምህርት ጽህፈት ቤት ኃላፊዎችን ጨምሮ ርዕሳነ መምህራን እና ሱፐርቫይዘሮች በተገኙበት ላለፉት ሶስት ቀናት ሲያካሂድ የቆየው ውይይት ተጠናቀቀ።

by | ዜና

ሀምሌ 17/2016 ዓ.ም) የውይይቱ ተሳታፊዎች ቢሮው ባቀረበው የ2016 ዓ.ም አፈጻጸምና በ2017 ዓ.ም መሪ እቅድ በቡድን በመሆን ባደረጉት ሰፊ ውይይት የተነሱ አስተያየቶችና የተለያዩ ማብራሪያ የሚፈልጉ ጥያቄዎች በክፍለ ከተማ ትምህርት ጽህፈት ቤት ኃላፊዎች አማካይነት ቀርቦ በአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱ እና በምክትል ቢሮ ኃላፊዎች ምላሽ ተሰጥቷል።

በውይይቱ ከተነሱ ሀሳቦች መካከል የተማሪዎችን ውጤትና ስነምግባር ለማሻሻል በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤት መመዝገቡ ፣ በትምህርት ለትውልድ ንቅናቄ በርካታ ተቋማት መገንባታቸው ፣ የብዝሀ ቋንቋ ተግባራዊ መሆኑ ፣ በትምህርት ቤቶች የከተማ ግብርና ተግባራዊ መደረግ መጀመሩ ፣ የርዕሳነ መምህራን ሪፎርም መካሄዱ ፣ ዘንድሮ የተማሪዎች የመማሪያ መጽሀፍ ወቅቱን ጠብቆ በበቂ ሁኔታ ተደራሽ መደረጉ ፣ መምህራንን የቤት ባለቤት ለማድረግ በማህበር የማደራጀት ስራ መጀመሩ እንዲሁም ዘንድሮ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ስርአት በአግባቡ መስፈኑ በጥንካሬ ከተነሱ ሀሳቦች መካከል የሚገኙ ሲሆን በማስፋፊያ አከባቢዎች ባለ የመማሪያ ክፍል እጥረት ምክንያት የተማሪ ክፍል ጥምርታው ከስታንዳርዱ ጋር አለመጣጣሙ ፣ አዲሱን ስርአተ ትምህርት መሰረት አድርገው ተግባራዊ በሆኑ አዳዲስ የትምህርት አይነቶች በሙያው የሰለጠኑ መምህራን አለመኖራቸው ፣ ከቅድመ አንደኛ ደረጃ ውጪ በሌሎች የትምህርት እርከኖች የመምህራን የሙያ ማሻሻያ ትምህርት እየተሰጠ አለመሆኑ ፣  የማታ ትምህርት ተማሪዎችን በሚፈለገው ደረጃ ውጤታማ እንዲሆኑ ትኩረት ቢደረግ ፣ የልዩ ፍላጎት ትምህርት ተማሪዎች ቁጥር እየጨመረ ቢሆንም በቂ ባለሙያ ቢመደብና አስፈላጊ ቁሳቁሶችን የማሟላቱ ተግባር ተጠናክሮ ቢቀጥል የሚሉ ሀሳቦች በቀጣይ ትኩረት እንዲሰጥባቸው ከተነሱ መካከል የሚጠቀሱ ናቸው።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱ በመርሀ ግብሩ ማጠቃለያ ባስተላለፉት መልዕክት በውይይቱ የተነሱ ፍሬያማና ገንቢ ሀሳቦች መሰረት በማድረግ በ2017 ዓ.ም የትምህርት አመት ከባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ በመሆን ውጤታማ ስራ እንደሚሰራ አስታውቀዋል።

ዶክተር ዘላለም አያይዘውም በ2017 ዓ.ም የትምህርት ዘመን የተማሪዎችን ውጤትና ስነ ምግባር በማሻሻል ሁለንተናዊ ስብዕናው የተገነባ ትውልድ ለማሻሻል በሚከናወኑ የተለያዩ ተግባራት ውጤታማነት በየደረጃው የሚገኙ የትምህርት አመራሮችም ሆኑ ባለሙያዎች የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ከፍተኛ በመሆኑ ከወዲሁ ተገቢውን የቅድመ ዝግጅት ስራ መስራት እንደሚገባቸው በመግለጽ ቢሮውም ከዝግጅት ምዕራፍ ጀምሮ የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል።

0 Comments

Submit a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *