የተማሪዎች የሒሳብና እንግሊዘኛ ትምህርት ውጤት እንዲጎለብት የርዕሳነ መምህራን ሚና ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ፡፡

by | ዜና

(መስከረም 6/2017 ዓ.ም) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ከ1ኛ እስከ 12ኛ ክፍል የሚማሩ ተማሪዎች በሒሳብና እንግሊዘኛ የትምህርት አይነቶች ውጤታማ እንዲሆኑ ባዘጋጀው ስትራቴጂክ እቅድ ዙሪያ የሚያደርገውን ውይይት በመቀጠል በዛሬው እለት ከዋና እና ከመማር ማስተማር ምክትል ርእሳነ መምህራን ጋር ውይይት አካሂዷል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ እና የቢሮ ኃላፊ ተወካይ ወይዘሮ ታጋይቱ አባቡ በመርሀ ግብሩ መክፈቻ ባስተላለፉት መልዕክት ስትራቴጂክ ዕቅዱ በ2016 ዓ.ም በየትምህርት አይነቱ የነበረውን የ6ኛ እና የ8ኛ ክፍል የተማሪዎችን የውጤት ትንተና መነሻ አድርጎ መዘጋጀቱን ጠቁመው በውጤት ትንተናው መሰረት ተማሪዎቹ በሒሳብና እንግሊዘኛ የትምህርት አይነቶች ያስመዘገቡት ውጤት አጥጋቢ ባለመሆኑ በስትራቴጂክ እቅዱ መዘጋጀቱን በመግለጽ ርዕሳነ መምህራን በስትራቴጂው በመቀመጡ ዝርዝር ተግባራት መሰረት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ በመወጣት ተማሪዎችን በሁለቱ የትምህርት አይነቶቹ ውጤታማ ማድረግ እንደሚገባቸው አመላክተዋል።

የተማሪዎች ውጤት መሻሻል እያሳየ ቢገኝም በሒሳብና እንግሊዘኛ የትምህርት አይነቶች የሚፈለገው ውጤት እየተመዘገበ ባለመሆኑ ቢሮው ተማሪዎች በሁለቱ የትምህርት አይነቶች ውጤታማ እንዲሆኑ ስትራቴጂ ነድፎ ወደ ተግባር መግባቱን ምክትል ቢሮ ኃላፊው አቶ አሊ ከማል ገልጸው ርዕሳነ መምህራን ተማሪዎች በሁለቱ የትምህርት አይነቶች የሚፈለገውን ውጤት ማስመዝገብ እንዲችሉ ለመምህራን አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል።

ከ1ኛ እስከ 12ኛ ክፍል የሚማሩ ተማሪዎች በሒሳብና እንግሊዘኛ የትምህርት አይነቶች ውጤታማ እንዲሆኑ የተዘጋጀው ስትራቴጂክ እቅድ የአጠቃላይ ትምህርት መረጃ ዝግጅትና አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በሆኑት በዶክተር ቢኒያም አወቀ እና በአጠቃላይ ትምህርት ሱፐርቪዥን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በሆኑት በአቶ አብዱልበር መሀመድ አማካይነት ቀርቦ ውይይት ከመካሄዱ ባሻገር ለተነሱ አስተያየቶችና ጥያቄዎች በኃላፊዎች ምላሽ ተሰቷል።

0 Comments