ቀን 30/9/2014 ዓ.ም

የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ጽህፈት ቤት በክፍለ ከተማው በሚገኙ የመንግስትና የግል ትምህርት ቤቶች የተዘጋጀ የሳይንስና የሒሳብ ትምህርቶች የፈጠራ ስራ አውደ ርዕይ በክፍለ ከተማው አስተዳደር ቅጥር ግቢ ውስጥ አካሄደ።

በአውደ ርዕዩ ተማሪዎች በሳይንስና ሒሳብ ትምህርቶች፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በስዕልና ቅርጻ ቅርጽ እንዲሁም በተለያዩ የስነ ጽሁፍ ስራዎች የሰሩዋቸው የፈጠራ ውጤቶች ቀርበው በተለያዩ አካላት ተጎብኝተዋል።

በመርሀ ግብሩ መክፈቻ የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ትምህርት ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሳምራዊተ ቅባቱ ባስተላለፉት መልዕክት ተማሪዎች በክፍል ውስጥ በንድፈ ሀሳብ የሚማሩትን ትምህርት ወደ ተግባር ቀይረው በዚህ መልኩ የፈጠራ ስራዎቻቸውን ለዕይታ ማቅረባቸው ለሀገራችን ሁለንተናዊ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ተግባር መሆኑን ጠቁመው በክፍለ ከተማ ደረጃ የተሻለ የፈጠራ ስራ ማቅረብ የቻሉ ተማሪዎች በከተማ ደረጃ በሚካሄደው ተመሳሳይ ፕሮግራም ተሳታፊ እንደሚሆኑ ገልጸዋል።

የክፍለ ከተማው ዋና አፈ ጉባኤ አቶ በቀለ ጉታ በበኩላቸው ተማሪዎችም ሆኑ መምህራን የሚሰሩት የፈጠራ ስራ የሀገሪቱን መሰረታዊ ችግር መቅረፍ የሚያስችል ተግባር መሆኑን ገልጸው የክፍለ ከተማው አስተዳደርም ለትምህርት ሴክተሩ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል።

አውደ ርዕዩን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ አማካሪ ወይዘሮ አበበች ነጋሽ እና ሌሎቭ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ያስጀመሩ ሲሆን ተማሪዎቹም የፈጠራ ስራዎቻቸውን ለክብር እንግዶቹና ለሌሎች አካላት አስጎብኝተዋል፡፡

በመርሃ ግብሩ ማጠቃለያም ከወዳደቁ እቃዎች ተመልሰዉ በተሰሩ የፈጠራ ስራዎች ፣ በሳይንስ ፣ በቴክኖሎጂ ፣ በግጥም ፣በስነ-ጽሁፍ ፣በመነባንብ እና በውዝዋዜ አሽናፊ ለሆኑ አካላት ዋንጫ እና ስርተፊኬት ተብርክቶላቸዋል፡፡