አዲስ አበባ ነሀሴ 29/2015 ዓ.ም ኦረንቴሽኑን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ የስርአተ ትምህርት ማበልጸግና ትግበራ ዳይሬክቶሬት አማካይነት የተዘጋጀ ሲሆን ኦረንቴሽኑ በቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት መጽሀፍ ዝግጅት ለተሳተፉ እና በዘርፉ ከፍተኛ ልምድ ያላቸው መምህራንን ጨምሮ በግብረገብ መጽሀፍ የትርጉም ስራ ተሳታፊ ለነበሩ መምህራን ነው የተሰጠው፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ የስርአተ ትምህርት ማበልጸግና ትግበራ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ታለማ በመርሀ ግብሩ ባስተላለፉት መልዕክት አዲሱን ስርአተ ትምህርት መሰረት በማድረግ የስርአተ ትምህርት ክለሳ ከተካሄደባቸው የትምህርት እርከኖች መካከከል አንዱ የቅድመ መደበኛ ትምህርት እንደመሆኑ መምህራኑ ከመጽሀፉ ይዘት ጋር በተገናኘ በቂ ግንዛቤ ይዘው ወደ መማር ማስተማር ስራው መግባት እንዲችሉ በማሰብ የመጽሀፉን ይዘት ለሚያስተዋውቁ አሰልጣኞች ኦረንቴሽን መስጠት ማስፈለጉን አስታውቀዋል፡፡
ከግብረገብ ትምህርት ጋር በተገናኘም በአዲሱ ስርአተ ትምህርት 1ኛ ደረጃ ለሚማሩ ተማሪዎች የአከባቢያቸውን ነባራዊ ሁኔታና ሀገር በቀል እውቀቶችን ታሳቢ ያደረገ መጽሀፍ ተዘጋጅቶ ከ2016ዓ.ም ጀምሮ ወደ ትግበራ እንደሚገባ ገልጸው በትምህርት አይነቱ የተዘጋጀውን የመጽሀፍ ይዘት ለመምህራኑ ማስተዋወቅ ትምህርቱን በአግባቡ ተግባራዊ ለማድረግ እንደሚረዳም አስረድተዋል፡፡
በዛሬው ኦረንቴሽን ተሳታፊ የሆኑ የመጽሀፍቱ አስተዋዋቂዎች ከመጪው ሀሙስ ጀምሮ ከየትምህርት ቤቱ ለተውጣጡ መምህራን የመጽሀፎቹን ይዘት የሚያስተዋውቁበት ፕሮግራም መዘጋጀቱን ከስራ ክፍሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
0 Comments